አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት በመሆን ተሾሙ

  

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 15፣ 2011 (ኤፍ.ቢ.ሲ) አምባሳደር ሳህለወቅርቅ ዘውዴ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት በመሆን በዛሬው ዕለት ተሾሙ።

አምባሳደር ሳህለወርቅ በ2ኛው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የፌዴሬሽን ምክር ቤት የጋራ ስብሰባ ላይ ነው ፕሬዚዳንት በመሆን የተሾሙት።

አምባሳደሯ በኢትዮጵያ ታሪክ አራተኛዋና የመጀመሪያዋ ሴት የሀገሪቱ  ፕሬዚዳንት በመሆን በሁለቱ  ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ ላይ ተሹመዋል።

ሹመቱን ተከትሎ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱና አምባሳደር ሳህለወቅርቅ  የስልጣን ርክክብ አድርገዋል።

አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ትምህርታቸውን በፈረንሳይ ሞንትፕሊር ዩኒቨርሲቲ ነው የተማሩት።

የስራ ልምዳቸውን ስንመለከት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ1989 እስከ 1993 በሴኔጋል የኢትዮጵያ አምባሳደር በመሆን አገልግለዋል።

በፈረንጆቹ 1993 እስከ 2002 በጂቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር እና በምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት (ኢጋድ) የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ በመሆን አገልግለዋል።

በአውሮፓውያኑ ከ2002 እስከ 2006 ድረስ ደግሞ በፈረንሳይ የኢትዮጵያ አምባሳደር፣ በዩኔስኮ የኢትዮጵያ ተወካይ በቱኒዝያ እና በሞሮኮ የኢትዮጵያ በአምባሳደር በመሆን ሀገራቸውን አገልግለዋል።

በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽንና በአፍሪካ ህብረት የኢትዮጵያ ተወካይ በመሆን ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ፥ በኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር በመሆንም ሰርተዋል።

በመቀጠልም አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ በተባበሩት መንግስታት ስር የነበረው የተቀናጀው የሰላም አስከባሪ ኃይል ተወካይ በመሆን በመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ሰርተዋል።

አምባሳደር ሳህለወቅርቅ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ2011 ጀምሮ በኬንያ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በረዳት ዋና ፀሃፊ ማዕረግ ዋና ዳይሬክተር ሆነው በማገልገላይ ላይ ነበሩ፡፡

በቅርቡም አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሀፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ የአፍሪካ ህብረት ልዩ መልዕክተኛ ሆነው ተሾሙ በማገልገል ላይ ነበሩ።

አምባሳደር ሳህለወርቅ ከአማርኛ በተጨማሪ እንግሊዝኛ እና ፈረንሳይኛ ቋንቋን አቀላጥፈው ይናገራሉ።

© 2020 Sidama Media Network All rights reserved.